ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአሰልጣኙ ጋር ተለያይቷል

በዛሬው ዕለት ከቅዱስ ጊዮርጊስ ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርበው የነበሩት አሰልጣኝ ስቴዋርት ሀል ጥያቄያቸው ተቀባይነት ማግኘቱን ክለቡ በፌስቡክ ገፁ አስታውቋል።

እንግሊዛዊው አሰልጣኝ በዓመቱ መጀመርያ ፖርቱጋላዊው ቫዝ ፒንቶን ተክተው መንበሩን ተረክበው የነበረ ቢሆንም ቡድኑ በተደጋጋሚ ነጥቦች እየጣለ ከዋንጫው ፉክክሩ መራቁ የአሰልጣኙን ቆይታ ጥቃቄ ምልክት ውስጥ ከቶት ነበር። አሰልጣኙ ባሳለፍነው እሁድ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ደቡብ ፖሊስ በሜዳው ያለ ጎል አቻ ከተለያየበት ጨዋታ በኋላ በሰጡት አስተያየትም ሁሉንም የቡድኑን ተጫዋቾች በተለያየ ጊዜ ቢሞክሩም ለውጥ አለማምጣቱን ጠቅሰው “ክለቡን ወደ ፊት ለማራመድ እና ለክለቡ ጥቅም ስል ነገ የራሴን ውሳኔ እወስናለው። ” ማለታቸው የሚታወስ ነው።

ከመሪው መቐለ 70 እንደርታ በ9 ነጥቦች የራቀው ቅዱስ ጊዮርጊስ የስቴዋርት ሀልን ስንብት ተከትሎ በረዳት አሰልጣኙ ዘሪሁን ሸንገታ እየተመራ ቀሪዎቹን 6 የሊግ ጨዋታዎች እንደሚያጠናቅቅ አስታውቋል።