የፕሪምየር ሊጉ ዐቢይ ኮሚቴ ስብሰባ ሊያደርግ ነው

የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ውድድርን ለመምራት የተመረጡት ሰባቱ ዐቢይ ኮሚቴ አመራሮች በነገው ዕለት የመጀመርያ ስብሰባቸውን ያደርጋሉ።

የ2012 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግን ክለቦች ራሳቸውን ችለው እንዲመሩ በማሰብ ባሳለፍነው ሳምንት በኢሊሊ ሆቴል በተደረገ ምርጫ መቶአለቃ ፈቃደ ማሞ (ኢትዮጵያ ቡና) ሰብሳቢ ሆነው ሲመረጡ ምክትል ሰብሳቢ ዶ/ር ከሳቴ ለገሰ (ከመቐለ) ተመርጠዋል። አቶ እሸቱ ቢያድጎ (ከፋሲል)፣ አቶ አንበሴ መገርሳ (ከአዳማ)፣ አቶ አሰፋ ሀሲሶ (ከድቻ)፣ አቶ አንበሳው አውግቸው (ከድሬዳዋ) እና አቶ መንግስቱ ሳሳሞ (ከሲዳማ ቡና) በኮሚቴነት መመረጣቸው ይታወቃል።

የመጀመርያቸው በሆነው በዚህ ስብሰባ ላይ የ2012 የፕሪምየር ሊግ ውድድር መቼ እንደሚጀምር፣ የኮሚቴ አወቃቀር፣ የቢሮ የማቴሪያል እና ሰነድ ርክክብ በአጠቃላይ በቀጣይ ውድድሩን በምን መልኩ መመራት አለበት በሚሉ ጉዳዮች ዙርያ ነገ ከ03:00 ጀምሮ ፌዴሬሽኑ አዲስ በገዛው ህንፃ መሰብሰቢያ አደራሽ ላይ ሰፊ ውይይት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።


© ሶከር ኢትዮጵያ