የ2012 የሴቶች ፕሪምየር ሊግ የሚጀምርበት ቀን ይፋ ሆነ

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን የ2012 የውድድር ዘመን የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አንደኛ እና ሁለተኛ ዲቪዝዮን ውድድሮች የሚጀመርባቸውን ቀናት ይፋ አድርጓል።

በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ ሴቶች እግርኳስ ልማትና ውድድር ኮሚቴ ሰብሳቢ ሶፊያ አልማሙን ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት በማካሄድ ሁለቱ ሊጎች የሚጀመሩበት ቀን ይፋ አድርገዋል። በዚህም መሠረት አስራ ሁለት ክለቦችን እንደሚያሳትፍ የሚጠበቀው የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አንደኛ ዲቪዚዮን የዕጣ ማውጣት ሥነ-ስርዓት ኅዳር 13 የሚከናወን ሲሆን ኅዳር 27 ደግሞ ውድድሩ ይጀምራል ተብሏል፡፡ ዘጠኝ ክለቦችን ያሳትፋል የተባለው የሁለተኛ ዲቪዚዮን ውድድሩ ደግሞ የዕጣ ማውጣቱ ቀን ኅዳር 13 የሆነ ሲሆን ታህሳስ 18 ደግሞ ውድድሩ እንደሚጀመር ተገልጿል፡፡

በተለያዘ በአንደኛ ዱቪዚዮን የሚወዳደረው ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ ከበጀት እና ከቡድኔ አቅም ጋር በአንደኛ ዲቪዚዮን መወዳደር አልችልም በሁለተኛ ዲቪዚዮን እንድወዳደር ይፈቀድልኝ ሲል ለፌዴሬሽኑ ደብዳቤን አስገብቷል፡፡

ከአንደኛ ዲቪዝዮን የተውጣጡ ተጫዋቾችን ያካተተው የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በአሁኑ ወቅት በታንዛኒያ አስተናጋጅነት ለሚካሄደው የሴካፋ ሴቶች ዋንጫ በዝግጅት ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡


© ሶከር ኢትዮጵያ