ቅዱስ ጊዮርጊስ ራሱን ማጠናከር ጀምሯል

ፈረሰኞቹ አዳዲስ ሁለት ተጫዋቾችን ያስፈረሙ ሲሆን የነባሮችንም ውል አራዝመዋል፡፡
የሲዳማ ቡናው የመስመር አጥቂ አዲስ ግደይ እና የአዳማ ከተማው አማካይ ከነዓን ማርክነህ ናቸው የፈረሰኞቹ ንብረት የሆኑት፡፡

በ2006 ክረምት ወር ላይ የከፍተኛ ሊጉን ክለብ ስልጤ ወራቤን ከለቀቀ በኃላ በሲዳማ ቡና ያለፉትን አምስት ዓመታት በወጥ አቋሙ ማገልገል የቻለው አዲስ ግደይ ከክለቡ ጋርም ሆነ በግሉ መልካም ዓመታትን አሳልፏል፡፡ በተለይ ከ2010 ጀምሮ በፕሪምየር ሊጉ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት ዝርዝር ውስጥ ስሙን ሲያሰፍር የነበረው አዲስ ግደይ በይፋ አዲሱ የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫዋች ሆኗል፡፡

ሌላኛው የክለቡ አዲስ ፈራሚ ከነዓን ማርክነህ ነው፡፡ የአማካይ ስፍራ ተጫዋቹ ከነዓን የአዳማ ወጣት ቡድንን ከለቀቀ በኃላ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እና አዲስ አበባ ከተማ ተጫውቶ ያሳለፈ ሲሆን ከ2009 ጀምሮ ደግሞ በአሳዳጊ ክለቡ አዳማ ሲጫወት ቆይቶ ማረፊያውን ፈረሰኞቹ ቤት አድርጓል፡፡

ጊዮርጊሶች ከአዳዲስ ተጫዋቾች በተጨማሪ የአጥቂዎቹ ጌታነህ ከበደ፣ አቤል ያለው እና ተከላካዩ ሄኖክ አዱኛን ውል አራዝሟል፡፡

👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!


© ሶከር ኢትዮጵያ