የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ 1ኛ ዙር ሪፖርት እና ግምገማ ዛሬ ተካሄዷል

የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ አንደኛው ዙር ግምገማ የክለብ ተወካዮች ፣ የፌዴሬሽኑ አመራሮች እና ጋዜጠኞች በተገኙበት ዛሬ ከረፋድ ጀምሮ በኢትዮጵያ ሆቴል ተካሂዷል፡፡ የግምገማው ሪፖርት እና ከክለቦች የተነሱ አስተያየቶችን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

የ1ኛው ዙር አፈፃፀም ሪፖርት

የ1ኛው ዙር አፈፃጸም ሪፖርት በውድድር እና ስነስርአት ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ገብረስላሴ አማካኝነት የቀረበ ሲሆን በግማሽ አመቱ የተከናወኑ ስራዎችን አብራርተዋል፡፡
ከ1.2 ሚልዮን በላይ ህዝብ ጨዋታዎችን እንዲከታተል ማስቻሉ ፣ የከፍተኛ ሊግ ኮሚቴ በየሳምንቱ እንዲሰበሰብና ፈጣን ውሳኔዎች እንዲወስን መደረጉ እና ውድድሩ አዲስ እንደመሆኑ አዲስ የውድድር ደንብ መዘጋጀቱ በሪፖርቱ ከተጠቀሱ ነጥቦች ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
በአፈፃፁሙ ላይ ለኢትዮጵያ ከ20 አመት ብሄራዊ ቡድን በርካታ የከፍተኛ ሊግ ክለብ ተጫዋቾች መመረጣቸው ፣ መልካም ስፖርታዊ ጨዋነት እና የተሟሟቀ ፉክክር እንደጠንካራ ጎን መወሰዳቸው ሲገለፅ የፕሮግራም መራዘም ፣ በሜዳቸው የሚጫወቱ ቡድኖች ለእንግዶች የልምምድ ሜዳ ያለማዘጋጀት ፣ ቡድኖች በሚመሩበት ጊዜ የኳሶች እጥረት እንዲኖሩ ማድረግ እንደደካማ ጎን ተጠቅሷል፡፡

የዲሲፕሊን ኮሚቴ ሪፖርት

በዲሲፕሊን ኮሚቴ በኩል የቀረበው ሪፖርት እንደሚያመለክተው በአንደኛው ዙር በተካሄዱት 240 ጨዋታዎች 876 ቢጫ እና 34 ቀይ ካርዶች የተመዘዙ ሲሆን በምድብ ሀ 475 ቢጫ እና 15 ቀይ ፣ በምድብ ለ ደግሞ 401 ቢጫ ካርድ እና 19 የቀይ ካርዶች ተመዝግበዋል፡፡

በስፖርታዊ ጨዋነት ረገድ በምድብ ሀ ወልድያ በአንደና ደረጃ ላይ ሲቀመጥ አዲስ አበባ ፖሊስ በመጨረሻ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡ በምድብ ለ ደግሞ ናሽናል ሴሜንት በቀዳሚነት ሲቀመጥ ወራቤ ከተማ በመጨረሻ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
44 ተጫዋቾች ፣ አሰልጣኞች ፣ የቡድን መሪዎች እና ሌሎች የክለብ አባላት በዲሲፕሊን ጥሰት ምክንያት በድምሩ 70ሺህ ብር እና የ79 ጨዋታ ቅጣቶች ተጥሎባቸዋል፡፡ 12 ቡድኖች ላይ ደግሞ በድምሩ 165ሺህ ብር ቅጣት ተጥሏል፡፡

የዳኞች ኮሚቴ ሪፖርት

በዳኞች ኮሚቴ በቀረበው ሪፖርት መሰረት 37 ዋና እንዲሁም 65 ረዳት ዳኞች በድምሩ 165 ዳኞች የከፍተኛ ሊጉን ጨዋታዎች የዳኙ ሲሆን 29 ኮሚሽነሮችም ለውድድሮቹ ተመድበዋል፡፡ አንድ ዋና ዳኛ ያጫወተው ከፍተኛ የጨዋታ ቁጥር 8 ሲሆን ዝቅተኛው 3 ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ ረዳት ዳኛ ደግሞ ከፍተናው 11 ሲሆን ዝቅተኛው 3 ሆኖ ተመዝግቧል፡፡

ከክለቦች የተሰጡ አስተያየቶች

በሪፖርቱ በርካታ ጠንካራ እና ደካማ ጎኖች የቀረቡ ሲሆን ከክለቦችም በርካታ አስተያየቶች እና በ2ኛው ዙር ትኩረት ሊደረግባቸው የሚገቡ ጉዳዮችን አንስተዋል፡፡ ከነዚህም መካከል ዋና ዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡-

-ተመልካችን ወደ አላስፈላጊ ስሜት ውስጥ የሚከቱ ዳኞች መኖራቸው ሊታሰብበት ይገባል፡፡
-ውድድሮች በተያዘላቸው ትክክለኛ ጊዜ እና ቦታ ማካሄድ ይገባል፡፡
-ከ20 አመት በታች ብሄራዊ ቡድን በተመረጡ ተጫዋቾች ዙርያ ግልጽ መስፈርት መኖር ይኖርበታል፡፡ ከሁሉም ክለብ ሁለትሁለት ተጫዋቾች በመምረጥ ውድድሩ እንዳይቋረጥ መደረግ ይርበታል፡፡
– የሁለተኛው ዙር ፕሮግራም ራቅ ያሉ ክለቦችን ያማከለ አይደለም፡፡
-የዳኞች ምደባ የተሰባጠረ መሆን ይኖርበታል፡፡
-ውድድሩ የሀገሪቱ 2ኛ ትልቅ ሊግ እንደመሆኑ የሚድያ ሽፋን ከዚህም በላይ ማደግ አለበት፡፡
-የዲሲፕሊን የገንዘብ ቅጣቱ ከፍተኛ ነው፡፡
-ኮሚሽነሮች ሪፖርታቸው ገለልተኛ እና ግልፅ መሆን ይኖርበታል፡፡
-የተስተካካይ ጨዋታዎች ሚዛናዊ አይደሉም፡፡ የአንድ ቡድን ጨዋታ ለሌላ ጊዜ ከተላለፈ አተቃላይ የሳምንቱ ጨዋታዎች አብረው መተላለፍ አለባቸው፡፡

የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የ2ኛ ዙር በመጪው ግንቦት 9 የሚጀምር ሲሆን በሐምሌ 18 ቀን 2008 ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ለማስታወስ ያህል የ1ኛው ዙር የደረጃ ሰንጠረዥ እና ከፍተኛ ግብ አግቢዎች ይህንን ይመስላሉ፡፡

ምድብ ሀ

picsart_1462722866831.jpg

ምድብ ለ

picsart_1462722945783.jpg

ከፍተኛ ግብ አግቢዎች

image

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *