የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ 2ኛ ዙር ዛሬ ይጀምራል፡፡ ከምድብ ሀ አንፃር በመሪዎቹ እና በተከታዮቹ መካከል ቀለል ያለ ፉክክር እየታየበት በሚገኘው ምድብ ለ ከ1-3 ደረጃን ይዘው ያጠናቀቁት ጅማ አባ ቡና ፣ አአ ከተማ እና ሀላባ ከተማ አሰልጣኞች ለሶከር ኢትዮጵየያ የሰጡትን አስተያየት እነሆ፡-
‹‹ወደ ፕሪሚየር መግባታችንን እስክናረጋግጥ ከወዲሁ ጨርሰናል ብለን አንዘናጋም። ›› ደረጄ – ጅማ አባ ቡና
የጅማ አባ ቡና ጥንካሬ ምስጢር
‹‹ የጥንካሬያችን ሚስጥሩ በቡድኑ ውስጥ ነፃነት መኖሩ ነው፡፡ ስራህን በነፃነት ስትሰራ ስኬታማ ትሆናለህ፡፡ ሌላው ተጫዋቾቻችን ወጣት በመሆናቸውና በየጨዋታው ለማሸነፍ በፍላጎት ስለሚጫወቱ ነው፡፡››
በንጸጽር ደካማ የሆነው የሜዳ ሪከርድ
‹‹ የደጋፊው ከፍተኛ ጉጉት አለ፡፡ ውጤቱን ከመፈለጉ የተነሳ መልካም የሚባል ጫና ያሳድራል ። ተጫዋቾቼም ደጋፊውን ለማስደሰት በሚያደርጉት ጥረት ውስጥ ስሜትና ጉጉት ውስጥ ይገቡና ስህተቶች ይፈጠራሉ፡፡ በዚህ ምክንያት እንጂ ነጥብ በጣልንባቸው ጨዋታዎች ተጋጣሚዎቻችን ከእኛ ተሽለው አይደለም፡፡ በሁለተኛው ዙር ይህ አስተካክለን እንገባለን ››
በሁለተኛው ዙር…
“በአንደኛው ዙር የነበረንን ጥንክሬ አስጠብቀን እንሄዳለን በአንዳንድ ቦታ ቡድናችንን ለማጠናከር አማካኝ ቦታ አበባየሁ ዮሃንስን ከሆሳህና ፣ በአጥቂ ቦታ አብርሃም ከመከላከያ ተስፋ ቡድን ፣ በተከላካይ ቦታ አቡቲን ከሰበታ አስመጥተናል”
የሁለተኛውን ዙር መጀመርያ ጨዋታዎች አለማድረጋቸው የሚፈጥረው ተጽእኖ
‹‹ ምንም የሚፈጥርብን ችግር የለም፡፡ እኔ ሆንኩ አጠቃላይ የቡድኑ አባላት ከክለባችን 5 ተጨዋቾች ለ20 አመት በታች ብሄራዊ በመመረጣቸው ደስተኛ ነን ። በአንደኛው ዙርም እንዲህ ያለ ነገር አጋጥሞን በአሸናፊነት ተወተናል፤ልምምዳችንን በአግባቡ በማድረግ እና ሌሎች ማድረግ የሚገቡን እያደረግን ውድድሩን እጠብቃለን፡፡ ››
በርካቶች ጅማ አባ ቡናን ለፕሪሚየር ሊግ መገመታቸው የሚያሳድርባቸው ጫና…
‹‹ ጅማ አባ ቡና ፕሪሚየር ሊግ ይገባል ብሎ መገመት ይቻላል፡፡ ይህ የአስትያየት ሰጪዎቹ መብት ነው። ነገር ግን እኛ ገብተናል ብለን አንዘናጋም። ሁሌም ለተጫዋቾቼ ይህ ሀሳብ ትክክል እንዳልሆነ እነግረቸዋለው፡፡ በእግር ኳስ የሚፈጠረው አይታወቅም፡፡ ባርሴሎና ላሊጋውን በ11 ነጥብ ልዩነት ይመራ ነበር፡፡ ነገር ግን በኋላ የተፈጠረውን አይተናል፡፡ ስለዚህ ገብተን ካልሆነ በስተቀር ከወዲሁ ጨርሰናል ብለን አንዘናጋም። ››
“…ወደ ፕሪሚየር ሊግ የምንገባ ይመስላል፡፡ ነገር ግን እያንዳንዱን ጨዋታ በጥንቃቄ እንጫወታለን” ስዩም ከበደ – አዲስ አበባ ከተማ
ከጨዋታ ጨዋታ መውረድ እና ለማሸነፍ መቸገር…
‹‹ መሠረታዊ የሆነ ጥያቄ ነው። አሁን እያዘጋጀሁት ያለ ቴክኒካል የግምገማ ሪፖርት አለ፡፡ ይሄም አሁን ባነሳችሁት ድክመታችን ላይ ያተኩራል፡፡ በሚገባ ኳሱን ተቆጣጥረን እንጫወታለን፡፡ ነገር ግን አጨራረስ ላይ ድክመት አለብን፡፡ ስል አጥቂዎች ባለመያዛችን በየጨዋታው 3 እና 4 ጎሎችን ማስቆጠር እየቻልን ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ይህን ክፍተታችንን ለመቅረፍ ከድሬድዋ ከተማ ፍቃዱ አለሙን አምጥተናል፡፡ ጥሩ ነገር ይሰራል የሚል እምነት አለን፡፡ ”
የመጀመርያዎቹን ጨዋታዎችን አለመድረጋቸው የሚፈጥረው ተጽእኖ
‹‹ አንዳንድ ጊዜ ውድድር መንፈሱን ጠብቆ አለመሄዱ ችግር አለው፡፡ እነዚህ የሚያልፉን ውድድሮች በኋላ ተደራራቢ ጨዋታን ሊያመጡ ይችላሉ ። ውድድሩ በተከታታይ ቢሄድ ጥሩ ነበር፣ ይህ ካልሆነ የሚመጣውን በሂደት እናየዋለን፡፡ በአጠቃላይ ሁለተኛው ዙር ላይ በጥንቃቄ ዕቅዳችንን ለማሳካት እንሰራለን፡፡
የአአ ከተማ ጉዞ መጨረሻ ፕሪሚየር ሊግ ነው ስለሚሉ ግምቶች…
“እንደ ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ ስናስበው ባርሴሎና በረጅም ርቀት ይመራ ነበር፡፡ በኋላ ላይ አንገት ለአንገት ሆነው ነው የጨረሱት፡፡ በእግር ኳስ የማይሆን ነገር የለም፡፡ በእርግጥ ከሦስተኛው ቡድን በሰባት ነጥብ እንርቃለን ፤ ከመሪውም በአንድ ጨዋታ ነጥብ ልዩነት ብቻ ነው ያነስነው፡፡ ይህ ማለት በስነ ልቦናው ጠንክረን እያንዳንዱን ጨዋታ በጥንቃቄ ማድረግ ይገባል። ነጥብ በጣልክ ቁጥር ከታች ያሉት እያሸነፉ የሚመጡ ከሆነ የሚያሳድረው ተፅእኖ ቀላል አይደለም። በካልኩሌሽን ከሆነ የምንገባ ይመስላል፡፡ ሆኖም በእግር ኳስ የማይሆን ነገር ስለሌለ በጥንቃቄ የምናየው ይሆናል፡፡ ”
” ወደ ፕሪሚየር ሊግ የመግባት ህልማችንን እናሳካለን” አላምረው – ሀላባ ከተማ
በሰፊ ነጥብ የራቁት ጅማ አባ ቡና እና አአ ከተማ ላይ ስለመድረስ
” በሚገባ የተዘጋጀንበት ነገር ነው። በሁለተኛ ዙር ላይ ከተጫዋቾቻችን እና አመራሮቻችን ጋር ትኩረት ሰጥተን ተወያይተንበታል፡፡ ወደ ፕሪሚየር ሊግ መግባት እንፈልጋለን፡፡ ለዚህም የሚረዱን ተጨዋቾች ፕሪሚየር ሊግ ከሚጫወቱ ክለቦች ለማስመጣት በድርድር ላይ እንገኛለን ይሄም እናሳካዋለን። አብዛኛው ከአንድ እስከ ሰባት ያሉ ቡድኖችን በሜዳችን የምንጫወት በመሆኑ የሜዳ ላይ አድቫቴጃችንን ለመጠቀምና ከሜዳ ውጪ ያሉብንን ጨዋታዎች ውጤት አስጠብቀን እንመለሳለን፡፡ በእርግጠኝነት ፕሪሚየር ሊግ የመግባት ህልማችንን እናሳካለን። ”
በርካታ ወሳኝ ተጫዋቾች ለቀው የውድድር ዘመኑን መጀመራቸው. .
” ወሳኝ የሆኑ ተጫዋቾች ነው ያጣነው፡፡ በዚህም የፈጠረብን ክፍተት አለ፡፡ ሆኖም እነሱን በሚገባ ሊተኩ የሚችሉ ተጫዋቾችን አምጥተናል፡፡ እነዚህን ተጫዋቾች ከነባሮቹ ጋር ለማዋሃድ ጊዜ ወስዶብናል፡፡ በአሁን ሰአት ከጨዋታ ጨዋታ እየተዋሃዱ ጥሩ እንቅስቃሴ እያደረጉ ነው ጥሩ ነገርም ይሰራሉ፡፡ “