አዲስ አበባ ከተማ ወልድያን አስተናግዶ 1 አቻ ተለያይቷል፡፡ ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ የሁለቱም ክለቦች አሰልጣኞች ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ ስለጨዋታው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
“በሁለተኛው አጋማሽ ብዙ ነገር ለማስተካከል ገብተናል” የአአ ከተማ አሰልጣኝ ስዩም ከበደ
ስለጨዋታው
“የመጨረሻ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ብንችል በዚህ ስሌት ነው የመጣነው፡፡ እንግዲህ ኳስ ጨዋታ በስህተት የታጀበ ነው፡፡ ለእረፍት ልንወጣ ሲል የገባው ግብ በራሳችን ስህተት ነው፡፡ በሁለተኛው አጋማሽ ብዙ ነገር ለማስተካከል ገብተናል፡፡ አሁንም ማሸነፍ እንደሚቻል ነው ስንናገር የነበረው፡፡ ለልጆቼም ልላቸው የምፈልገው ይህንን ነበር፡፡ ከእረፍት በኃላ ጥሩ ነበር፡፡ ቢያንስ ነጥብ ተጋርተው መውጣታችን ያደረጉት ጥረት መልካም ነገር ስለሆነ በጥሩ ጎን አየዋለው፡፡”
ቀጣይ እቅድ
“እኛ ቀደም ብለን መስራት አስበን እየሰራን ነው ያለነው፡፡ ምክንያቱም ብዙ ክፍተት ቦታዎች ላይ አሉን፡፡ የተጎዱ ተጫዋቾች በርካታ ናቸው፡፡ አሁንም ወሳኝ ቦታ ላይ በተለይ አጨራረስ ላይ የምንፈልጋቸው ተጫዋቾች ነበሩ 4 ልጆች ጥሩ አግኝተናል ብዬ አስባለው፡፡ ከውጪ የመጡት ቡድናችንን ተቀላቅለው ሁለተኛውን ዙር ጠንካራ እንደምንሆን እርግጠኛ ነኝ፡፡ በዚህ ስሌት ሁለተኛውን ዙር ለመስራት እና ለመዘጋጀት እየሞከርን ያለነው፡፡ መስተዳደሩም ከፍተኛ እግዛ አድርጓልናል፡፡ የተቻለንን ስርተን ቡድኑ የሚቆይበትን መንገድ እንፈልጋለን ማለት ነው፡፡”
“ትንሽ ደከም ብለን የታየነው መሃል ክፍሉ አከባቢ ነው” የወልዲያ አሰልጣኝ ንጉሴ ደስታ
ስለጨዋታው
“ሰሞኑን ካደረግናቸው ጨዋታዎች ትንሽ ወረድ ብለናል፡፡ ዛሬ ሶስት ነጥብ ማግኘት ነበረብን፡፡ እንደጠበቅነው አልሆነም፡፡ ግን ያገኘነው ውጤት ጥሩ ነው፡፡”
“ትንሽ ደከም ብለን የታየነው መሃል ክፍሉ አከባቢ ነው፡፡ ትንሽ መሃል ክፍሉ ላይ ልጆችን ለመቀየር ስለፈኩ ትንሽ እሱ ላይ ትኩረት ያደረኩት፡፡ (የአጥቂ ክፍሉ) ጥሩ ስለነበር እና ግቦች እያስቆጠር ስለሚገኝ ለውጥ ለማድረግ አልፈለግንም፡፡”
ስለአንደኛ ዙር
“ከከፍተኛ ሊጉ እንደመምጣታችን ያገኘነው ውጤት እና የያዝነው ደረጃ በጣም ጥሩ ብዬ ነው የማስቀምጠው፡፡ ከመነሻውም የተሟላ ዝግጅት አላደረግንም፡፡ ግን ልምድ ያላቸው ተጫዋቾች እንደመሆናቸው እየተሻሻሉ መጠን አሁን በነበረው ሁኔታ ላይ ጥሩ እንቅስቃሴ እያደረግን ነው የመጣነው፡፡ ብዙ ያጣናቸው እና ነጥብ የጣልንባቸው ሁኔታዎች አሉ፡፡ ትንሽ ተከላካይ ክፍላችን ጥሩ ነው፡፡ የማጥቃት እንቅስቃሴያችን ትንሽ ቀዝቀዝ ያለነው እና በሁለተኛው ዙር ላይ ተሻሽለን ተስተካክለን ግዜ የለንም በርግጥ እዛ ላይ ሰርተን እንመጣለን፡፡”