ቅዱስ ጊዮርጊስ በቶታል 2017ካፍ ቻምፒየንስ ሊግ ቅድመ ማጣሪያ ከሜዳው ውጪ ኮት ዲኦር ይገጥማል፡፡ የቡድኑ አምበል ደጉ ደበበ ስለዝግጅታቸው እና ስለጨዋታው የሚከተለው አስተያየት ሰጥቷል፡፡
ስለዝግጅት
“ዝግጅታችንን የጀመርነው አምና 2008 ሊጉን ካሸነፍን በኃለ ነው፡፡ ከክረምት ጀምሮ ስንዘጋጅ የነበረው ለፕሪምየር ሊጉ እና ቻምፒየንስ ሊጉ ነው፡፡ በፕሪምየር ሊጉም ሆነ በቻምፒየንስ ሊጉም ረጅም መጓዝ ነው የምናስበው፡፡ እንደተጫዋችም ቢሆን የክለቡ ፍላጎት እና እራይ በቻምፒየንስ ሊግ ስምንቱ ውስጥ ገብቶ የማየት እና አንድ ታሪክ የመስራት ፍላጎት ነው ያለን፡፡ በየአመቱ እንሳተፋለን ሳይሳካልን ይቀራል፡፡ በየዓመቱ ስህተቶቻችንን እየቀነስን ጥሩ ጎናችንን እያሰፋን ዘንድሮም የተሻለ ጉዞ እንሄዳለን ብዬ ነው ማስበው፡፡”
ስለጨዋታው
“እያንዳንዱን ውድድር በጥንቃቄ ነው የምንጫወተው፡፡ ደርሶ መልስ ጨዋታ ስለሆነ ከተሳሳትክ ረጅም ጉዞ የለውም፡፡ ደርሶ መልስ ጨዋታ ነው ስህተትህን ቀንሰህ አሸንፈን የምንሄድበትን ብቻ ነው የምናስበው፡፡ እንደሊግ ረጅም ጉዞ ቢሆን ስህተትህን ከቀን ወደቀን እያስተካከልክ ትመጣለህ፡፡ ግን የደርሶ መልስ ጨዋታ ስለሆነ ጥንቃቄን ይፈልጋል፡፡”
“ኳስ ጨዋታ ሁሌም ባለፈ ታሪክ ሳይሆን ወቅታዊ አቋም ነው ሁሌም፡፡ በኳስ ጨዋታ ዛሬ ያሸነፈከው ቡድን ነገ ልታሸንፈው አትችልም ሁሌም፡፡ እራስን አቋም አሻሽለህ 90 ደቂቃ እራስህን በማዘጋጀት ነው ለማሸንፍ የምንጥረው እንጂ ያለፈው ታሪክ ጥሩ አይደለም እና እኛ ደግሞ እራሳችንን ከፍ አድርገን እነሱን ዝቅ አድርገን የምናይበት መንገድ የለም፡፡ እንደቡድን ከበሬታ እንሰጣቸዋለን፡፡ አስተካከለን እንደቡድን የምንሄድበትን መንገድ ብቻ ነው የምናስበው፡፡”
የምድብ ጉዞ
“እኛም ለዚሁ መሳካት እንሰራለን ብዬ ነው ማስበው፡፡ በ2009 ከምናስባቸው አንዱ ፕሮግራም ነው፡፡ እንደተጫዋችም እንደቡድንም የምናስበው ቻምፒየንስ ሊጉ ላይ ስምንቱ ውስጥ ገብተን ተፎካካሪ መሆን ነው የምናስበው፡፡ ይህ ነው እቅዳችን፡፡”