ኢትዮጵያ ቡና ሁለት ካሜሩናውን እና አንድ ኢትዮጵያዊ ተጫዋች ማስፈረሙን አስታውቋል፡፡ በክለቡ የሚገኙ የውች ዜጎች ቁጥርም 4 ካሜሩናውያንን ጨምሮ 5 ደርሷል፡፡ ለቡና የፈረሙት ተጫዋቾች አጥቂዎቹ ንዳኒ ፋይስ ፣ ፓትሪክ ኦኮሌ እና አማካዩ ኤርሚያስ በለጠ ናቸው፡፡
በሊባኖስ ሊግ ለሚወዳደረው ሻባብ አል-ጋዜህ ክለብ በመጫወት 2015 የውድድር ዘመንን ያሳለፈው ንዳኒ ፋይስ ለክለቡ 8 ጨዋታዎች አድርጎ ምንም ግብ ማስቆጠር አልቻለም፡፡ ሌላው ካሜሩናዊ ፓትሪክ ኦኬሌ ዛሬ ክለቡ በንግድ ባንክ 2-1 በተሸነፈበት የወዳጅነት ጨዋታ ተሰልፎ የተጫወተ ሲሆን ለቡና ከመፈረሙ በፊት ስላለው የእግርኳስ ህይወቱ በቂ መረጃ ማግኘት አልቻልንም፡፡ ከየመኑ አል ሳቅር ክለብ የፈረመው ኤርሚያስ በለጠ በተከላካይ አማካይ ስፍራ የሚጫወት ሲሆን እንደ ፓትሪክ ሁሉ ዛሬ ክለቡ ከባንክ ባደረገው የወዳጅነት ጨዋታ ላይ ተቀይሮ ገብቶ ተጫውቷል፡፡
ኢትዮጵያ ቡና ሁለቱን አጥቂዎች ማስፈረሙን ተከትሎ በቡድኑ የሚገኙት የውጭ ዜጎችን ቁጥር 5 አድርሷል፡፡ በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት ግብ ጠባቂውን ሀሪሰን ሀዎሲ ፣ ካሜሩናዊው ተከላካይ ፊቨር ኦኪ እና የቀድሞው ጂኤስኤም ቤጅያ እና ዋይዳድ ተልመን አጥቂ ዊልያም ያቤውን ማስፈረሙ የሚታወስ ነው፡፡
ምስል – ከላይ ፓትሪክ ኦኬሌ ፣ ከታች ኤርሚያስ በለጠ