አዳነ ግርማ እና ምንተስኖት አዳነ ስለ ሸገር ደርቢ. . .

ኢትዮጵያ ቡና ቅዱስ ጊዮርጊስን የሚያስተናግድበት የስምንተኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ጨዋታ ዕሁድ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይደረጋል፡፡ ቦሌ በሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ የልምምድ ስፍራ የተገኘችው ሶከር ኢትዮጵያ 2ኛ አምበሉ አዳነ ግርማ እና ምንተስኖት አዳነን ስለሸገር ደርቢ አናግራለች፡፡

“እኛ የበላይነታችንን ማሳየት ብቻ ነው የምንፈልገው” አዳነ ግርማ

 

ስለጨዋታው

“ሁላችንም መስከረም ላይ ነው የምንዘጋጀው፡፡ የተለየ ጨዋታ ብዬ አላስብም፡፡ በርግጥ የስፖርት ቤተሰቡ ትልቅ ትኩረት ይሰጠዋል፡፡ እኛ ደግሞ ወደ አሸናፊነቱ መጥተናል፡፡ ሶስት ጨዋታ ላይ ጥሩ አልነብርንም፡፡ ይህንን አሸናፊነታችንን ይዘን እንቀጥላለን ብዬ ነው የማስበው፡፡ ጥሩ ጨዋታ እንደሚሆን ምኞቴ ነው፡፡”

የኢትዮጵያ ቡና ጥሩ ያልሆነ የውድድር ዘመን ጅማሮ

“በየትኛውም አጋጣሚ ቢሆን እኛ ወረድን ቡና ወጣ ደርቢ ስለሆነ ይህ ሊገልፀው አይችልም፡፡ ጨዋታው ደርቢ ስለሆነ ትኩረት ይሰጠዋል፡፡ እነሱም ቀላል ተጋጣሚ ይሆናሉ ብዬ አላስብም፡፡ ይህ ደረጃ አያስጨንቀንም፡፡ እኛ የበላይነታችንን ማሳየት ብቻ ነው የምንፈልገው፡፡ ሁሌም ጊዮርጊስ በሁሉም ነገሮች የበላይ ሆኖ ነው ማጠናቀቅ የሚፈልገው፡፡ ከዚህ አንፃር አሁን ጥሩ አይደሉም እና ከእኛ ጋር ጥሩ አይሆኑም ብዬ አልጠብቅም፡፡ 90 ደቂቃው እስኪያልቅ ድረስ ለማሸነፍ እንጥራለን ፤ እነሱም እንደዚያው፡፡ ወደአሸናፊነቱ መጥተናል ፤ እናሸንፋለን ብዬ ነው የማስበው፡፡”

“ከዚህ በፊት ያየሃቸው ጨዋታዎች የዕለቱን ጨዋታ አይወስኑም” ምንተስኖት አዳነ

ስለዝግጅት

“ዝግጅታችንን እንዳያችሁት በሚገባ ሁኔታ አድርገናል፡፡ ከሌላ ጊዜ የተለየ ዝግጅት እያደረግን አይደለም፡፡ በቀን አንድ ጊዜ ነው ልምምድ የምንሰራው፡፡ ይህንን ሰሞን እንደዛ ነበር ስናደርግ የነበረው፡፡ እኔም ትኩረት ሰጥቼ በሚገባ እየተዘጋጀው ነው፡፡”

ስለጨዋታው

“ከዚህ በፊት ያየሃቸው ጨዋታዎች የዕለቱን ጨዋታ አይወስኑም፡፡ ጨዋታው ላይ ምንም እንደሚገጥም አታውቅም ፤ የተለየ ነገር ሊገጥምህ ይችላል፡፡ ኢትዮጵያ ቡና ግብ የማግባት ችግር አለበት ተብሎ እየተነገረ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ነገር ከእኛ ጋር ይፈጠራል ብዬ አላስብም፡፡ ብዙ ግዜ የደርቢ ጨዋታ እንደተጫዋች ሆነህ ስታየው መጫወት የምትፈልገው ጨዋታ ነው፡፡ እንደተመልካችም ስታየው መመልከት የምትፈልገው ጨዋታ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ሲገናኙ ደግሞ ብዙ ህዝብ የሚከታተለው ጨዋታ ነው፡፡ ብዙ ትኩረት ይሰጠዋል፡፡ ይኸው ሳምንት ሙሉ እንዳየኸው ትኩረት ይሰጠዋል፡፡”

ከመከላከል ተነስቶ ስለማጥቃት

“በእርግጥ አማካይ ተጫዋችም እያለው ግቦችን አስቆጥር ነበር፡፡ በተፈጥሮ ፣ ከታች ጀምሮ ሳድግም የተጫወትኩት የተከላካይ አማካይ ሆኜ ነበር፡፡ ግን በባህሪዬ ትንሽ ማጥቃት ላይ አተኩራለው፡፡ ይህ ነገር ጠቅሞኛል ብዬ አስባለው፡፡ ተከላካይም ሆኜ አሰልጣኙ የኔን ብቃት ተረድቶ የማጥቃት አጋጣሚ ሳገኝ እንዳጠቃ ስለፈቀደልኝ ነው ይህንን እያደረክኩ ያለሁት፡፡ ቡድኑም ተጠቅሟል ብዬ አስባለው፡፡”

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *