የሴካፋ ዞን የቻምፒየንስ ሊግ ማጣሪያ ጨዋታዎች ተራዝመዋል

ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሚሳተፍበት የሴካፋ ዞን የቻምፒየንስ ሊግ ማጣሪያ ውድድር ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል።

በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚደረገው የአፍሪካ ሴቶች ቻምፒየንስ ሊግ ውድድር በቀጣይ ዓመት በግብፅ ይደረጋል። የአህጉሪቱ ሀገራት የሊግ አሸናፊዎችም በስድስት ቀጠና ተከፋፍለው የማጣሪያ ጨዋታዎችን እንዲያደርጉ መርሐ-ግብር ተይዞ ነበር። በሴካፋ ዞን የሚደረገው ውድድር ከአራት ቀናት በኋላ በኬንያ አስተናጋጅነት እንደሚጀመር ቢገለፅም ውድድሩ መራዘሙ ታውቋል።

ስለዚህም ለውድድሩ ዝግጅቱን በቢሾፍቱ ከተማ ሲያደርግ የነበረው የ2013 የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አሸናፊው ክለብ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ወደ በተያዘው ጊዜ መሠረት ወደ ኬንያ እንደማይጓዝ ታውቋል።