ፕሪሚየር ሊግ ፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ቻምፒዮንነት እየተጠጋ ነው

 

በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 22ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ መሪነቱን ሲያሰፋ ሲዳማ ቡና እና ኢትዮጵያ ቡና እና ንግድ ባንክ በቁልቁል ጉዟቸው ቀጥለዋል፡፡

በአዲስ አበባ ስታድየም ቅዱስ ጊዮርጊስ ኤሌክትሪክን 1-0 በማሸነፍ ወደ ቻምፒዮንነቱ ተጠግቷል፡፡ የፈረሰኞቹን የድል ግብ አዳነ ግርማ በ65ኛው ደቂ ከመረብ አሳርፏል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ድሉን ተከትሎ በ45 ነጥብ ከተከታዩ ሲዳማ ቡና በ7 ነጥቦች ርቆ ወደ ቻምፒዮንነት የሚያደርገውን ጉዞ አጠናክሯል፡፡

አዲስ አበባ ስታድየም ላይ ሙገር ሲሚንቶን ያስተናገደው ደደቢት 2-1 አሸንፏል፡፡ የደደቢትን የድል ግብ ሳሙኤል ሳኑሚ በ33ኛው ደቂቃ ከመረብ አሳርፏል፡፡ ደደቢት በድሉ ታግዞ ቅዱስ ጊዮርጊስን በርቀት መከተል ጀምሯል፡፡ ሙገር በአንፃሩ በ19 ነጥቦች የመውረድ አፋፍ ላይ ተገኝቷል፡፡

ቦዲቲ ላይ ሲዳማ ቡናን ያስተናገደው ወላይታ ድቻ 2-1 አሸንፏል፡፡ ዮሴፍ ዴንጌቶ እና አላዛር ፋሲካ ለባለሜዳው የድል ግቦቹን ሲያስቆጥሩ ብሩክ አየለ የሲዳማን ግብ አስቆጥሯል፡፡ ሲዳማ ሽንፈቱን ተከትሎ ከመሪው ቅዱስ ጊዮርጊስ ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ 7 ሲሰፋ የቻምፒዮንነት ተስፋውም ጨልሟል፡፡

አዳማ አበበ ቢቂላ ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ያስተናገደው አዳማ ከነማ 4-2 በማሸነፍ በድንቅ ግስጋሴው ቀጥሏል፡፡ የውድድር ዘመኑ አጋማሽ ክስተት የሆው ዮናታን ከበደ 3 ግቦች አስቆጥሮ ሀት-ትሪክ ሲሰራ ዳኛቸው በቀለ ቀሪዋን ግብ ከመረብ አሳርፏል፡፡ ሲሳይ ቶሊ እና አኪም አካንዴ የባንክን ግቦች ከመረብ አሳርፈዋል፡፡

ሀዋሳ ላይ ኢትዮጵያ ቡናን ያስተናገደው ሀዋሳ ከነማ 2-0 በማሸነፍ ከወራጅ ቀጠናው መራቅ የሚያስችለውን ውጤት አግኝቷል፡፡ የሀዋሳ ከነማን የድል ግቦች ታፈሰ ተስፋዬ እና ጋዲሳ መብራቴ ከመረብ አሳርፈዋል፡፡

ወደ አርባንጭ የተጓዘው ዳሽን ቢራም በድል ተመልሶ ከወራጅነት ስጋቱ በ9 ነጥቦች ርቋል፡፡ ሚካኤል ጆርጅ እና ኤርሚያስ ኃይሉ የዳሽንን የድል ግብ ከመረብ ሲያሳርፉ ተሸመ ታደሰ የአርባንጭን ግብ አስቆጥሯል፡፡

መልካ ቆሌ ላይ መከላከያን ያስተናገደው ወልድያ 1-0 ተሸንፏል፡፡ ሳሙኤል ታዬ የጦሩን ብቸኛ ግብ ከመረብ አሳርፏል፡፡ ወልድያዎች ከመውረድ ለመትረፍ ቀሪዎቹን 4 ጨዋታዎች በሙሉ ማሸነፍ የሚጠበቅባቸው ሲሆን በ24 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ኤሌክትሪክ ሁሉንም ጨዋታ መሸነፍ ይጠበቅበታል፡፡

 

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *