የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከቦትስዋና ጋር ለሚያደርገው የወዳጅነት ጨዋታ መስከረም 17 ወደ ስፍራው ያመራል፡፡ ጨዋታው የሚደረገው መስከረም 19 ሲሆን በማግስቱ ብሄራዊ ቡድናችን ወደ አዲስ አበባ ይመለሳል፡፡
የኢትዮጵያ ከ20 አመት በታች ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ከቡርኪና ፋሶ ጋር ሊያደርገው የነበረው የአለም ከ20 አመት በታች ሴቶች የማጣርያ ጨዋታ መሰረዙን ካፍ አስታውቋል፡፡ ጨዋታው ወደፊት ይካሄድ አይካሄድ ወይም ለኢትዮጵያ ፎርፌ ይሰጥ አይሰጥ የታወቀ ነገር የለም፡፡
የከፍተኛ ሊግ እና ብሄራዊ ሊግ ጨምሮ ሌሎች የውስጥ ውድድሮች በቅርብ ጊዜያት የሚጀመሩ አይመስልም፡፡ የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ህዳር 4 ሊጀመር ይችላል ቢባልም እስካሁን አልተረጋገጠም፡፡ ከ17 አመት በታች ፕሪሚር ሊግ ፣ ከፍተኛ ሊግ እና ብሄራዊ ሊጉ እንዴት እና በምን አይነት መልኩ እደሚካሄድም እስካሁን አልታወቀም፡፡
ፌዴሬሽኑ እንዳስታወቀው አዲስ ለተቋቋመው ከፍተኛ ሊግ የክለቦች እና የተጫዋቾች ምዝገባ ገና ያልተካሄደ ሲሆን በቅርቡ ምዝገባው ይጀመራል ተብሏል፡፡
ከምዝገባው በኋላ ውድድሩ አዲስ በመሆኑ ከክለቦች ጋር ውይይት ተደርጎለት በምን ያህል ዞን እንደሚከፈል ሲወሰን የውድድሩ ደንብ እና ስርአትም ይዘጋጅለታል፡፡