አይቮሪኮስታዊው አጥቂ ከፈረሰኞቹ ጋር ተለያየ

ቅዱስ ጊዮርጊስ በጥቅምት ወር አጋማሽ የተቀላቀለው የፊት መስመር ተጫዋቹ ዛቦ ቴጉይ በስምምነት ከክለቡ ጋር መለያየቱን አስታውቋል፡፡

የ29 ዓመቱ አጥቂ ከጋናው ክለብ አሻንቲ ኮቶኮ የ5 ወራት ቆይታ በኋላ በዓመቱ መጀመርያ ቅዱስ ጊዮርጊስ የተቀላቀለ ሲሆን በአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ ቢያደርግም በሊጉ ተፅዕኖ መፍጠር ባለመቻሉ በተጠባባቂ ወንበር ላይ ለማሳለፍ ተገዷል። ቀሪ ኮንትራት እያለውም በጋራ ስምምነት ከክለቡ ተለያይቷል፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ቅዱስ ጊዮርጊስ የሚያስመጣቸው የውጪ ተጫዋቾች ስኬታማ መሆን እየተሳናቸው ሲሆን ከፓትሪክ ማታሲ እና ኤድዊን ፍሪምፖንግ ውጪ አመዛኞቹ ፈራሚዎች የውል ጊዜያቸውን ከማጠናቀቃቸው በፊት ክለቡን ሲለቁ ተስተውሏል።

© ሶከር ኢትዮጵያ