ሀድያ ሆሳዕና የሦስት ወጣት ተጫዋቾችን ውል አራዝሟል

በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ መሪነት የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን እያደረጉ የሚገኙት ሀድያ ሆሳዕናዎች የሦስት ተጫዋቾቻቸውን ውል አድሰዋል።

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የቀጣይ ዓመት ተሳትፎአቸውን በአዲሱ አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ እየተመሩ ወደ ውድድር የሚገቡት ሀድያ ሆሳዕናዎች አዳዲስ እና ነባር ተጫዋቾችን በመያዝ በሆሳዕና ከተማ ዝግጅታቸውን እየከወኑ የሚገኙ ሲሆን በክለቡ ያሉ ሦስት ወጣት ተጫዋቾችን ውል ለተጨማሪ ዓመት ቡድኑ አድሷል።

በሆሳዕና ከተማ በክረምት ወቅት በሚደረገው የያሆዴ ዋንጫ ላይ ጥሩ ሲንቀሳስ በአሰልጣኝ ያሬድ ገመቹ ዕይታ ውስጥ ገብቶ የተጠናቀቀውን ዓመት ቁልፍ ሚናን ለቡድኑ ሲወጣ የነበረው የአማካይ ስፍራ ተጫዋቹ ብሩክ ማርቆስ አንድ አመት ቢኖረውም ተጨማሪ አንድ አመት በመጨመር ውሉን ሲያራዝም ከታችኛው የሀድያ ሆሳዕና ቡድን የተገኙት እና በ2013 አጋማሽ ላይ ወደ ዋናው ቡድን ያደጉት የመስመር አጥቂው ተመስገን ብርሀኑ እና የግራ መስመር ተከላካዩ ካሌብ በየነ የስድስት ወራት ቀሪ ውል ቢኖራቸውም ተጨማሪ የስድስት ወራት ውል አክለው ፈርመዋል።