ከፍተኛ ሊግ | ስልጤ ወራቤ አዲስ አሰልጣኝ ቀጥሯል

በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ምድብ ሀ ስር የሚገኘው ስልጤ ወራቤ የአዲስ አሰልጣኝ ቅጥርን ፈፅሟል።

በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ በምድብ ሀ ስር ተደልድሎ የ2016 የውድድር ዘመንን እያደረገ የሚገኘው ስልጤ ወራቤ የውድድር ዘመኑን በአሰልጣኝ ኑሩ መሐመድ እየተመራ በሊጉ እየተሳተፈ የሚገኝ ሲሆን እስከ አሁን ባደረጋቸው ሰባት የምድቡ ጨዋታዎች ባስመዘገባቸው ውጤቶች በደረጃ ሰንጠረዡ ግርጌ ላይ በ3 ነጥቦች መቀመጡን ተከትሎ የአሰልጣኝ ለውጥ ለማድረግ በመወሰኑ ክለቡ በትናንትናው ዕለት አሰልጣኝ ፀጋዬ ወንድሙን በቦታው ሾሟል።

የቀድሞው የኢትዮጵያ መድን እና አቃቂ ቃሊቲ አሰልጣኝ የነበሩት አሰልጣኝ ፀጋዬ በ2015 ሻሸመኔን ከተማን በመረከብ ከከፍተኛ ሊጉ ቡድኑን ወደ ፕሪምየር ሊግ አሳድገው ከቡድኑ ጋር በያዝነው የውድድር ዓመት ድረስ ቆይታን አድርገው ከወራት በፊት ከክለቡ ጋር የተለያዩ ሲሆን አሁን ደግሞ የከፍተኛ ሊጉ ስልጤ ወራቤን ለማሰልጠን ክለቡን በኃላፊነት መረከባቸውን ክለቡ ለሶከር ኢትዮጵያ አሳውቋል።