ሙጂብ ቃሲም ለወራት ከሜዳ ይርቃል

በቅርቡ የጣና ሞገዶቹን የተቀላቀለው አጥቂው ሙጂብ ቃሲም በህመም ምክንያት ለወራት ከሜዳ እንደሚርቅ ታውቋል።

በትናትናው ምሽት ባህር ዳር ከተማ በሃያ ሁለተኛ ሳምንት ከሀድያ ሆሳዕና ጋር ያለ ጎል በአቻ ውጤት በተጠናቀቀው ጨዋታ ከዕረፍት መልስ አጥቂው ሙጂብ ቃሲም ከበድ ያለ ህመም አጋጥሞት ከሜዳ ተቀይሮ የወጣ ሲሆን ለተሻለ ህክምና በአንቡላንስ ወደ ሆስፒታል መሄዱም ይታወቃል።

ማታውኑ ህክምናውን ያደረገው ሙጂብ ትከሻው ላይ ስብራት እንዳጋጠመው ታውቋል። ይህን ተከትሎ ህክምናውን በአግባቡ ተከታትሎ ወደ ሜዳ ለመመለስ ወራቶች እንደሚያስፈልጉት ሰምተናል።

በጉዳት እና በተለያዩ ምክንያቶች የተጫዋቾቹን ግልጋሎት በበቂ ሁኔታ እያገኘ ያልሆነው ባህር ዳር ከተማ የሙጂብ ቃሲም ለረጅም ጊዜ በህመም ከሜዳ መራቅ ሌላ ፈተና እንደሚሆን ይጠበቃል።