ቅድመ ዳሰሳ | ድሬዳዋ ከተማ ከ ኢትዮጵያ ቡና

በድሬዳዋ ስታዲየም የሚደረገው የድሬዳዋ ከተማ እና የኢትዮጵያ ቡና ጨዋታን እንደሚከተለው ዳሰነዋል።

የስምዖን ዓባይ ቡድን በ4ኛ ሳምንት የሊጉ ጨዋታ ወደ ባህር ዳር አቅንቶ የደረሰበትን የ4-1 ሽንፈት ለማካካስ አልሞ ነገ ወደ ሜዳ ይገባል። የተደራጀ የተከላካይ መስመር እንደሌለው የታየው ቡድኑ በሊጉ ከሚሳተፉ 16 ክለቦች ከፍተኛ ግብ በማስተናገድ ቀዳሚው ነው(11)። ነገም ቡድኑ በያዘው የተፍረከረከ የተከላካይ ክፍሉ ከሰሞኑ ከፍተኛ መነቃቃት ላይ የሚገኘውን የኢትዮጵያ ቡና ጥቃት ለማቆም ሊቸገር እንደሚችል ተገምቷል። ከዚህ ውጪ ቡድኑ ከማጥቃት ወደ መከላከል በሚያደርጋቸው የዘገዩ ሽግግሮች ክፍተቶችን ለተጋጣሚ ሊሰጥ እንደሚችል ይታሰባል። በተለይ ይህ ጉዳይ ባሳለፍነው ሳምንት በባህር ዳር ሽንፈት ሲያስተናግድ በጉልህ ታይቷል።

ቡድኑ ካለበት የመከላከል ድክመት እና ከተጋጣሚው የጨዋታ ዘይቤ የተነሳ ከባለፈው ሳምንት የተጨዋች አደራደር ቅርፁ (ፎርሜሽን) ለውጦችን እንደሚያደርግ ይጠበቃል። ምክንያቱም ኢትዮጵያ ቡናዎች በኳስ ቁጥጥር የጨዋታውን ሚዛን ወደ ራሳቸው ለማድረግ ስለሚጥሩ ቡድኑ የመሃል ሜዳ ተጨዋቾችን እንደሚያበዛ ይታመናል። ይህም ሂደት ቡድኑ በጨዋታው ብልጫ እንዳይወሰድበት ያደርጋል ተብሎ ይታሰባል። ቡድኑ የመከላከል ችግሮች ቢኖሩበትም የነገው ጨዋታ በሜዳው እንደመሆኑ ችግሮቹ በመጠኑ ሊሸፈኑ እንደሚችሉ ይታሰባል። ከዚህ በተጨማሪም ቡድኑ ከጨዋታዎች ርቆ የነበረውን አምበሉ ሳምሶን አሰፋ ነገ ሊያገኝ ስለሚችል መነቃቃቶች ሊኖሩ ይችላሉ።

ምንም የተጨዋች ቅጣት የሌለበት ቡድኑ ያሬድ ሃሰን እና ሳምሶን አሰፋን (መሰለፉ ቢያጠራጥርም) ከጉዳት ሲያገኝ ምንያህል ተሾመ እና ረመዳን ናስርን በተቃራኒው ከስብስቡ ውጪ አድርጓል።

ከጨዋታ ጨዋታ መሻሻል እያሰየ የሚገኘው የካሳዬ አራጌው ኢትዮጵያ ቡና ባሳለፍነው ሳምንት ከፍፁም የጨዋታ ብልጫ ጋር ሃዋሳ ከተማን ማሸነፍ ይታወሳል። ቡድኑ በመጨረሻ ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች ከወትሮው በተለየ ወደፊት የሚደረጉ የኳስ ቅብብሎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ ለድሬዳዋ ፈታኝ ሊሆን እንደሚችል ያሳያል። በተለይ በሃዋሳው ጨዋታ ሲጠቀምበት የነበረው የተደራጀ የማጥቃት ሂደት ለቡድኑ ግርማ ሞገስን አጎናፅፎታል። የሜዳውን ስፋት በመስመር አጥቂዎቻቸው የሚጠቀሙት ኢትዮጵያ ቡናዎች የተጋጣሚን (ድሬዳዋ ከተማ) የመከላከል አደረጃጀት ሊረብሽ እንደሚችል ተገምቷል። ከዚህ የመስመር አጨዋወት በዘለለ የፊት መስመር ተጨዋቾቹ ፍጥነት እና ቅልጥፍና ነገም ቡድኑን ሊጠቅም እንደሚችል ይጠበቃል።

ምንም እንኳን ቡድኑ ከጨዋታ ጨዋታ እየተሻሻለ ቢመጣም ኳስ ከግብ ክልሉ ጀምሮ ለመመስረት የሚያደርገው ጥረት አደጋዎችን ራሱ ላይ ሊጋብዙ በሚችሉ መንገዶች እንደሆነ ታይቷል። ከዚህ የተነሳ የድሬዳዋ ተጨዋቾች ተጭነው የሚጫወቱ ከሆነ በጎ ነገሮችን ለቡድናቸው ሊያመጡ ይችላሉ። ቡድኑ ካለበት የኳስ አመሰራረት ችግር በተጨማሪ የአጨራረስ ብቃቱ ነገ ዋጋ እንዳያስከፍለው ያሰጋል። ምንም እንኳን ቡድኑ ባሳለፍነው ሳምንት ሃዋሳን 4-1 ቢያሸንፍም በእለቱ ሲገኙ የነበሩ ጥሩ ጥሩ አጋጣሚዎችን ሲያመክን ታይቷል።

እንደ ባለሜዳዎቹ ሁሉ ምንም የቅጣት ዜና የሌለባቸው ቡናማዎቹ በነገው ጨዋታ የታፈሰ ሰለሞን እና የአቡበከር ናስርን ግልጋሎት ያገኛሉ።

እርስ በርስ ግንኙነት

– ሁለቱ ቡድኖች በሊጉ ለ16 ጊዜያት ያህል ተገናኝው ኢትዮጵያ ቡና ገሚሱን (8) በማሸነፍ የበላይ ሲሆን 5 ጊዜ አቻ ተለያይተው በ3 አጋጣሚዎች ድሬዳዋ ከተማ አሸንፏል።

– በ16ቱ ግንኙነቶች 39 ጎሎች ሲቆጠሩ 25 ጎሎች ቡናማዎቹ ያስቆጠሯቸው ናቸው። ቀሪዎቹ 14 ጎሎችን ብርቱካናማዎቹ አስቆጥረዋል።

ግምታዊ አሰላለፍ

ድሬዳዋ ከተማ (4-2-3-1)

ፍሬው ጌታሁን

ያሬድ ዘውድነህ – በረከት ሳሙኤል – ዘሪሁን አንሼቦ – አማረ በቀለ

አማኑኤል ተሾመ – ዋለልኝ ገብሬ

ያሬድ ታደሰ – ኤልያስ ማሞ – ሳሙኤል ዘሪሁን

ሪችሞንድ ኦዶንጎ

ኢትዮጵያ ቡና (4-3-3)

ተ/ማርያም ሻንቆ

አህመድ ረሺድ – ፈቱዲን ጀማል – ወንድሜነህ ደረጀ – አስራት ቱንጆ

ታፈሰ ሰለሞን – ዓለምአንተ ካሣ – አማኑኤል ዮሐንስ

አቤል ከበደ – እንዳለ ደባልቄ – አቡበከር ናስር


© ሶከር ኢትዮጵያ