ከፍተኛ ሊግ | ጅማ አባ ጅፋር በርካታ ተጫዋቾችን ወደ ስብስቡ ቀላቅሏል

የ2016 የከፍተኛ ሊግ ተሳታፊ የሆነው ጅማ አባ ጅፋር በርከት ያሉ አዳዲስ ተጫዋቾችን ዝውውር ሲያጠናቅቅ የነባሮቹንም ውል አድሷል።

በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ እና በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ላይ በርከት ያሉ ዓመታትን ያስቆጠረው ጅማ አባ ጅፋር ወደ ቀድሞ ስሙ ለመመለስ እና ለዘንድሮው የውድድር ዓመት ከፍተኛ የሆነ ዝግጅት በባቱ ከተማ እያከናወነ ሲሆን ለዚህ የውድድር ዘመንም ክለቡን ያጠናክራሉ ብሎ ያሰባቸውን በርከት ያሉ አዳዲስ ተጫዋቾች ወደ ስብስቡ ቀላቅሏል። ክለቡ የተወሰኑ ነበር ተጫዋቾቹን ውልም ማደስ ችሏል።

ተጫዋቾቹንም ስንመለከት ከዚህ በፊት የከፍተኛ ሊግ ልምድ ያላቸው የቀድሞው የኢትዮጵያ ቡና ፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ባሳለፍነው ዓመት በኮልፌ ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረው የአማካይ ስፍራ ተጫዋቹ ፊልሞን ገ/ፃዲቅ ፤ የይርጋ ጨፌ ቡና የፊት መስመር አጥቂ የነበረው ኢሳያስ ታደሰ ፤ ለኢትዮ ኤሌክትሪክ ፣ ሰበታ ከተማ ፣ ኢትዮጵያ መድን የተጫወተው እና ወደ ቀድሞ ክለቡ የተመለሰው ግብ ጠባቂው ቢኒያም ታከለ ፤ የፊት መስመር ተጫዋቹ አስቻለው ግርማ ከደብረ ብርሃን ከተማ ወደ ቀድሞ ክለቡ መመለስ ችሏል። በተጨማሪም ክለቡ በሻሸመኔ ከተማ ፣ ኦሜድላ እና ኢትዮጵያ መድን የተጫወተው የመስመር ተከላካዩ ጌትነት ታፈሰ ፣ በጅማ አባ ቡና ተስፋ እና አምቦ ከተማ ሲጫወት የነበረው የአጥቂ መስመር ተጫዋቹ ነቢል አብዱሰላም ፣ ከከፋ ቡና ተከላካዩን ተመስገን አማረን በዚህ  ክረምት የግሉ ማድረግ ችሏል።

በተጨማሪም ጅማ አባ ጅፋር አብረውት የነበሩት ግብ ጠባቂው ዮሐንስ በዛብህ ፣ የመሃል ተከላካዮቹ ባህሉ መሐመድ ፣ ናትናኤል በርሔ እና ልመንህ ታደሰን በተጨማሪም ክለቡ የግራ መስመር ተከላካዩን አቡበከር ኸይረዲንን ውል ለተጨማሪ ዓመት አራዝሟል።