የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ኮከቦች ምርጫ ዛሬ ምሽት ተካሄደ

በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ስር በተካሄዱ ስድስት የውድድር ዓይነቶች የ2011 ኮከቦች የሽልማት መርሃግብር ዛሬ ምሽቱን በካፒታል ሆቴልና ስፓ ተካሂዷል።

የ2011 ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ተጫዋቾችና አሰልጣኞች እጩዎች ከነበረባቸው ጨዋታ መልስ በመርሃግብሩ እንዲታደሙ በማሰብ ከተያዘለት ሰዓት እጅጉን ዘግይቶ በጀመረው በዚሁ መርሃግብር በፌደሪሽኑ ስር በሚካሄዱ ውድድሮች በዓመቱ የተሻለ አፈፃፀም የነበራቸው ተጫዋቾች አሰልጣኞችና ዳኞች እውቅና የተሰጠ ሲሆን ዘንድሮ በተለየ መልኩ የህይወት ዘመን እንዲሁም ልዩ ተሸላሚዎች ተካተውበት የኢፌድሪ ስፓርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ኤልያስ ሽኩር እንዲሁም የእግርኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት ኢሳይያስ ጂራን ጨምሮ በርከት ያሉ የስራአስፈፃሚ አባላት በተገኙበት በድምቀት ተካሂዷል።

መርሐግብሩን በንግግር የከፈቱት የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌደሬሽን ፕሬዚዳንት ኢሳይያስ ጅራ ይህ ሽልማት ተሸላሚዎችን ለማበረታት ብቻ ሳይሆን ሌሎች ዘንድሮ በሽልማት ውስጥ ያልተካተቱት ደግሞ በቀጣይ ይበልጥ ጠንክረው በመስራት የተሻለ የውድድር መንፈስ ለመፍጠር ታልሞ የሚካሄድ መሆኑን ገልጸዋል።

በሽልማት መርሐግብሩም በቅድሚያም በተለያዩ የውድድር አይነቶች በአመቱ በስፖርታዊ ጨዋነት ዘርፍ ተሸላሚዎች እውቅና የተሰጣቸው ሲሆን የተዘጋጀላቸውን የምስክር ወረቀት ከክብር እንግዶቹ በክብር ተቀብለዋል።

የስፖርታዊ ጨዋነት ዘርፍ አሸናፊዎች

ከ20 ዓመት በታች ፕሪምየር ሊግ – ፋሲል ከነማ
አንደኛ ሊግ – ጋሞ ጨንቻ
ከፍተኛ ሊግ – ቡራዩ ከተማ
ሴቶች ፕሪምየር ሊግ ሁለተኛ ዲቪዝዮን – መቐለ 70 እንደርታ
አንደኛ ዲቪዝዮን ሴቶች – ኢትዮ ኤሌክትሪክ
ወንዶች ፕሪምየር ሊግ – ፋሲል ከነማ

በመቀጠል በቅደም ተከተል በየውድድሩቹ የተሻሉ ለነበሩ ስፖርተኞችና ዳኞች ሽልማት በክብር እንግዶቹ የተበረከተ ሲሆን በዚህም

ከ20 ዓመት በታች ፕሪምየር ሊግ ተሸላሚዎች

የምስጋና እውቅና
1ኛ ወላይታ ድቻ
2ኛ መከላከያ
3ኛ ሀዋሳ ከተማ

-ምስጉን ዋና ዳኛ አብዲ ከድር
-ምስጉን ረዳት ዳኛ መኮንን ይመር
-ኮከብ ግብ አስቆጣሪ – ታምራት ስላስ (ወላይታ ድቻ)
-ኮከብ ግብጠባቂ – አቡሽ አበበ (ወላይታ ድቻ)
-ኮከብ አሰልጣኝ – ግዛቸው ጌታቸው (ወላይታ ድቻ)
-ኮከብ ተጫዋች – መስፍን ታፈሰ (ሀዋሳ ከተማ)

አንደኛ ሊግ

የምስጋና እውቅና
1ኛ ባቱ ከተማ
2ኛ ኮልፌ ቀራንዮ
3ኛ ጋሞ ጨንቻ

-ምስጉን ረዳት ዳኛ – ጌዲዮን ሄኖክ
-ምስጉን ዋና ዳኛ – ሙሉነህ አብዲ
-ኮከብ ጎል አስቆጣሪ – ቤዛ መድህን (ሀዲያ ሊሞ)
-ኮከብ ግብጠባቂ – ወንድወሰን ረጋሳ (ባቱ ከተማ)
-ኮከብ አሰልጣኝ – ቆፋ ኮርሜ (ባቱ ከተማ)
-ኮከብ ተጫዋች – ፈቱ አብደላ (ኮልፌ ቀራንዮ)

ሴቶች 2ኛ ዲቪዝዮን

የምስጋና እውቅና
1 አቃቂ ቃሊቲ
2 መቐለ 70 እንደርታ
3 ፋሲል ከነማ

-ኮከብ ግብ አስቆጣሪ – ዓለሚቱ ድሪባ (ሻሸመኔ)፣ ዮርዳኖስ በርኸ (መቐለ)
-ኮከብ ግብጠባቂ – ዓይናለም ሽታ (ቂርቆስ ክ/ከተማ)
-ኮከብ አሰልጣኝ – አቡዱራህማን ዑስማን (አቃቂ ቃሊቲ)
-ኮከብ ተጫዋች – ንግስቲ ኃይሉ (አቃቂ ቃሊቲ)

ከፍተኛ ሊግ

የምስጋና እውቅና
1-ሰበታ ከተማ/ወልቂጤ ከተማ/ሀዲያ ሆሳዕና
-ምስጉን ረዳት ዳኛ – ድሪባ ቀነኒሳ
-ምስጉን ዋና ዳኛ – ዓለማየሁ ለገሰ

-ኮከብ ጎል አስቆጣሪ – ስንታየሁ መንግስቱ (አርባምንጭ ከተማ)
-ኮከብ ግብጠባቂ – ጆርጅ ደስታ (ኢትዮጵያ መድን)
-ኮከብ ተጫዋች – ጌቱ ኃይለማርያም (ሰበታ ከተማ)
-ኮከብ አሰልጣኞች
ምድሀ ሀ አሰልጣኝ ክፍሌ ቦልተና (ሰበታ ከተማ)
ምድሀ ለ አሰልጣኝ ደረጀ በላይ (ወልቂጤ ከተማ)
ምድሀ ሐ አሰልጣኝ ግርማ ታደሠ (ሀዲያ ሆሳዕና)

የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አንደኛ ዲቪዝዮን

የምስጋና እውቅና
1 አዳማ ከተማ
2 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
3 መከላከያ

-ምስጉን ረዳት ዳኛ – ወይንሸት አበራ
-ምስጉን ዋና ዳኛ – ፀሀይነሽ አበበ
-ኮከብ ጎል አስቆጣሪ – ሴናፍ ዋቁማ (አዳማ ከተማ)
-ኮከብ ግብጠባቂ – እምወድሽ ይርጋሸዋ (አዳማ ከተማ)
-ኮከብ አሰልጣኝ – ሳሙኤል አበራ (አዳማ ከተማ)
-ኮከብ ተጫዋች – ሴናፍ ዋቁማ (አዳማ ከተማ)

የወንዶች ፕሪምየር ሊግ

የምስጋና እውቅና
1 መቀለ 70 እንደርታ
2 ሲዳማ ቡና
3 ፋሲል ከተማ

-ምስጉን ረዳት ዳኛ ኢንተርናሽናል ረዳት ዳኛ – ትግል ግዛው
-ምስጉን ዋና ዳኛ ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ – ቴዎድሮስ ምትኩ
-ኮከብ ጎል አስቆጣሪ – አማኑኤል ገ/ሚካኤል (መቐለ 70 እንደርታ)
-ኮከብ ግብጠባቂ – ፊሊፕ ኦቮኖ(መቀለ 70 እንደርታ)
-ኮከብ አሰልጣኝ – ገብረመድህን ኃይሌ(መቐለ 70 እንደርታ)
-ኮከብ ተጫዋች – ሱራፌል ዳኛቸው(ፋሲል ከነማ)

በተጨማሪም ሀገራችንን በተለያዩ ዓለምአቀፍ ውድድሮች ላይ በዳኝነት ያስጠሩት ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ሊዲያ ታፈሰ፣ ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ባምላክ ተሰማ ፣ኢንተርናሽናል ረዳት ዳኛ ተመስገን ሳሙኤልና እውቁ ፌዚዮቴራፒስት ይስሃቅ ሽፈራው በመርሃግብሩ ልዩ ተሸላሚ በመሆን እውቅና ተስቷቸዋል። በተጨማሪም የአፍሪካ እግርኳስ አባት ለሆኑት ክብር አቶ ይድነቃቸው ተሰማ የህይወት ዘመን ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። ሽልማቱን የተረከቡት ልጃቸው አቶ ታደለ ይድነቃቸው ባደረጉት ንግግር አባታቸውን ዋቢ በማድረግ ዝነኛ (ተሸላሚ) መሆን ቀላል እንደሆነና ዝነኛ ሆኖ መቀጠል ከባዱ ፈተና መሆኑን በማስታወስ ለተሸላሚዎች አደራ አዘል መልእክት አስተላልፈዋል።


© ሶከር ኢትዮጵያ